በሃገር ደረጃ ሲሰጥ የቆየው የሪሜድያል የማጠቃለያ ፈተና በሰላም ተጠናቀቀ።

በዓዲግራት ዩኒቨርሲቲ ሲሰጥ የቆየው የአቅም ማሻሻያ ትምህርት የማጠቃለያ ፈተና በሰላም ተጠናቀቀ። የፈተናውን መጠናቀቅ ተከትሎ የዓዲግራት ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ዶ/ር ገብረሚካኤል ወ/ገብርኤል የምስጋና መልዕክት አስተላልፈዋል።

ለፈተናው ዝግጅት ከተለያዩ ክፍሎች የተውጣጣ አብይ ግብረ ሀይል ተቋቁሞ ከዝግጅት ስራ ጀምሮ ፈተናው እስኪጠናቀቅ ድረስ ከፍተኛ ርብርብ መደረጉን እና ውጤታማ ስራዎች መከናወናቸውን የጠቆሙት ፕሬዝዳንቱ፣ ፈተናው ያለምንም የፀጥታ ችግር እንዲሁም ምንም አይነት የቴክኒክ ችግር ሳይኖር በሰላም መጠናቀቁን አስታውቀዋል።

ፕረዚዳንቱ በማከል በዚህ ሂደት የላቀ አዎንታዊ አስተዋጽኦ እያበረከቱ ላሉ ባለድርሻ አካላት በተለይም ለኢትዮቴሌኮም፣ ለከተማው ኤሌክትሪክ አገልግሎት፣ ለዩኒቨርስቲው መረጃና መገናኛ ቴክኖሎጂ ዳይሬክቶሬት፣ ለሰላምና ደህንንት አካላት፣ አመራርና ባለሙያዎች ዩኒቨርስቲው ከልብ የመነጨ ምስጋናና አክብሮት ያቀርባል ሲሉ ተናግረዋል።

ከነገ ጀምሮ ለሚካሄደው ሀገር አቀፍ የመውጫ ፈተና በቂ ዝግጅት መደረጉን ያወሱት ፕሬዝዳንቱ፣ የአቅም ማሻሻያ ትምህርት ማጠቃለያ ፈተና የተፈተኑ ተማሪዎች መልካም ውጤት እንዲገጥማቸው፣ ለመውጫ ፈተናው በዝግጅት ላይ የሚገኙ ተመራቂ ተማሪዎችም መልካም የፈተና ጊዜ እንዲሆንላቸው መልካም ምኞታቸውን ገልፀውላቸዋል።

የዓዲግራት ዩኒቨርሲቲ የፈተና ማዕከል ኃላፊ የሆኑት ታደሰ ብርሃነ(ረ/ፕሮፌሰር) በበኩላቸው፣ ዩኒቨርሲቲው በቂ ዝግጅት በማድረጉ እንዲሁም ተማሪዎች የፈተና ስርዓት አክብረው በመገኘታቸው ፈተናው በሰላምና በተሳካ ሁኔታ መጠናቀቁን ተናግረዋል።

በሃገር ደረጃ ለሚሰጠው መውጫ ፈተና ኣስመልክቶ በዓዲግራት ዩኒቨርስቲ ለተማሪዎች ኦሬንቴሽን ተሰጠ።

ዓዲግራት ዩኒቨርሲቲ ሰኔ 04/2018 ዓ.ም ጀምሮ የሚሰጠው የመጀመሪያ ድግሪ ተማሪዎች የመውጫ ፈተና (Exit Exam) አስመልክቶ የግንዛቤ መስጫ መድረክ ኣዘጋጀ።

በዓመቱ አጋማሽ የነበረ የመውጫ ፈተና በሃገር ደረጃ የተሻለ ውጤት እንደነበረና አሁንም ተደግሞ ለራሳችሁና ለዩኒቨርስቲው የምታኮሩ እንደምትሆኑ እተማመናለሁ ሲሉ የዩኒቨርስቲው አካዳሚክ ፕሮግራም ዳይሬክተሩ ግርማይ ታደለ(ረ/ፕሮፌሰር) በመክፈቻ ንግግራቸው ተናግረዋል።

በኦሬንቴሽኑ መርሃግብር ከፌደራል ትምህርት ምዘናና ፈተናዎች አገልግሎት የመጣው ኣቶ ጥላሁን ደሰለኝ ተማሪዎች ወደ ፈተና አዳራሽ ሲገቡ ለፈተና በወጣ መመርያ መሰረት የተፈቀዱና የተከለከሉ ነገሮችን በመለየት ተግባራዊ ማድረግ እንዳለባቸው መልእክት አስተላልፏል።

ተማሪዎች የማይፈቀዱ ነገሮችን በዶርም ትተው በመምጣት ፈተና በታቀደለት ግዜ ተጀምሮ እንዲጠናቀቅ ለፀጥታ ሓይሉ ድጋፍ ማድረግ እንደሚገባቸው በፌደራል ፖሊስ ዋና ኢንስፔክተር መዝገቡ ጋሹ ገልፀዋል።

ከወዲሁ ለውድ ተማሪዎቻችን መልካም እድል እንመኛለን!!